Widgetized Section

Go to Admin » Appearance » Widgets » and move Gabfire Widget: Social into that MastheadOverlay zone

የኢፌዴሪ ህገ መንግስት ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ምን ይላል?

efdre
አዲስ አበባ ፣ መስከረም 29 ፣ 2009 (ኤፍ ቢ ሲ) የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከትናንት ጀምሮ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጇል።
የኢፌዴሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 93 የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሚደነገግበትን ሁኔታ በዝርዝር ያስቀምጣል።
ምዕራፍ አስራ አንድ
ልዩ ልዩ ድንጋጌዎች
አንቀጽ 93
ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ

1 ሀ. የውጭ ወራሪ ሲያጋጥም ወይም ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን አደጋ ላይ የሚጥል ሁኔታ ሲከሰትና በተለመደው የህግ ማስከበር ስርዓት ለመቋቋም የማይቻል ሲሆን፣ ማናቸውም የተፈጥሮ አደጋ ሲያጋጥም ወይም የህዝብን ጤንነት አደጋ ላይ የሚጥል በሽታ ሲከሰት፥ የፌደራሉ መንግስት የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመደንገግ ስልጣን አለው።
ለ. የተፈጥሮ አደጋ ሲያጋጥም ወይም የህዝብን ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥል በሽታ ሲከሰት የክልል መስተዳድሮች በክልላቸው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሊያውጁ ይችላሉ። ዝርዝሩ ክልሎች ይህን ህገ መንግስት መሰረት በማድረግ በሚያወጧችው ህገ መንግስቶች ይወሰናል።
2 በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ 1/ሀ/ መሰረት የሚታወጅ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ፤
ሀ. የህዝብ ተወካዮቸ ምክር ቤት በስራ እያለ የታወጀ ከሆነ በታወጀ በአርባ ስምንት ሰዓታት ውስጥ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቅረብ አለበት፤ አዋጁ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሁለት ሶስተኛ ድምጽ ካላገኘ ወዲያውኑ ይሻራል።
ለ. ከላይ በንዑስ አንቀጽ /ሀ/ የተጠቀሰው እንደተጠበቀ ሆኖ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በስራ ላይ ባልሆነበት ወቅት የሚታወጅ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቅረብ ያለበት አዋጁ በታወጀ በአስራ አምስት ቀናት ውስጥ ነው።
3. በሚኒስትሮች ምክር ቤት የተደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በምክር ቤቱ ተቀባይነት ካገኘ በኋላ ሊቆይ የሚችለው እስከ ስድስት ወራት ነው። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሁለት ሶስተኛ ድምጽ አንድን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በየአራት ወሩ እንዲታደስ ሊያደርግ ይችላል።
4 ሀ. የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በሚታወጅበት ጊዜ የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣቸው ደንቦች መሰረት የሃገርን ሰላምና ህልውና፣ የህዝብን ደህንነት፣ ህግና ስርዓትን የማስከበር ስልጣን ይኖረዋል።
ለ. የሚኒስትሮች ምክር ቤት ስልጣን በህገ መንግስቱ የተቀመጡትን መሰረታዊ የፖለቲካና ዴሞክራሲ መብቶችን፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅን ለማወጅ ምክንያት የሆነውን ጉዳይ ለማስወገድ ተፈላጊ ሆኖ በተገኘው ደረጃ፣ እስከማገድ ሊደርስ የሚችል ነው።
ሐ. የሚኒስትሮች ምክር ቤት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስራ የሚያወጣቸው ድንጋጌዎችና የሚወስዳቸው እርምጃዎች በማናቸውም ረገድ በዚህ ህገ መንግስት አንቀጽ 1፣ 88፣ 25 እና 39፤ ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2 የተቀመጡትን መብቶች የሚገድቡ ሊሆኑ አይችሉም።
5. በሃገሪቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በሚታወጅበት ወቅት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከአባላቱና ከህግ ባለሙያዎች መርጦ የሚመድባቸው ሰባት አባላት ያሉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም መርማሪ ቦርድ ያቋቁማል፤ ቦርዱ አዋጁ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሚጸድቅበት ጊዜ ይቋቋማል።
6. የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም መርማሪ ቦርድ የሚከተሉት ስልጣንና ሃላፊነቶች አሉት፤
ሀ. በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ምክንያት የታሰሩትን ግለሰቦች ስም በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ይፋ ማድረግና የታሰሩበትን ምከንያት መግለጽ፤
ለ. በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወቅት የሚወሰዱት እርምጃዎች በማናቸውም ረገድ ኢ-ሰብዓዊ አለመሆናቸውን መቆጣጠርና መከታተል፤
ሐ. ማናቸውም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እርምጃ ኢ-ሰብዓዊ መሆኑን ሲያምንበት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወይም የሚኒስትሮች ምክር ቤት እርምጃውን እንዲያስተካክል ሃሳብ መስጠት፤
መ. በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እርምጃዎች ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት የሚፈጽሙትን ሁሉ ለፍርድ እንዲቀርቡ ማድረግ፤
ሠ. የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲቀጥል ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥያቄ ሲቀርብ ያለውን አስተያየት ለምክር ቤቱ ማቅረብ።