Widgetized Section

Go to Admin » Appearance » Widgets » and move Gabfire Widget: Social into that MastheadOverlay zone

አቶ ለማ መገርሳ የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳደር ሆነው ተሾሙ

leme-megersa
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 13፣ 2009 (ኤፍ.ቢ.ሲ)የጨፌ ኦሮሚያ ዛሬ ባካሄደው አምስተኛ የሥራ ዘመን ሁለተኛ ዓመት ሁለተኛ አስቸኳይ ስብሰባ የምክር ቤቱን አፈ ጉባኤና የክልሉን ርዕሰ መስተዳድ ጨምሮ የተለያዩ ሹመቶችን አፀደቀ።
የጨፌ ኦሮሚያ የክልሉ ርዕሰ ምስተዳደር እንዲሆኑ እጩ ሆነው የቀረቡትን የአቶ ለማ መገርሳን ሹመት በሙሉ ድምጽ ተቀብሎ አጽድቆታል።
ቀደም ሲል የጨፌው አፈ ጉባኤ ሆነው ሲያገለግሉ በነበሩት አቶ ለማ መገርሳ ምትክም የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር የነበሩት አቶ እሸቱ ደሴ አፈ ጉባኤ ሆነው ተመርጠዋል።
የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሆነው የተመረጡት አቶ ለማ መገርሳ ባደረጉት ንግግርም፥ “አሁን በተሰጠን ሀላፊነት በክልሉ የተጋረጡ ችግሮችን ከመፍታት ባለፈ ለእያንዳንድ የህብረተሰቡ ጥያቄ ፈጣን ምላሽ የመስጠት ሀላፊነት አለብን” ብለዋል።
ምንም እንኳ በክልሉ ፈጣን እድገት እየተመዘገበ እና በርካታ የስራ እድሎች እየተፈጠረ ቢሆንም የፍላጉቱን ያክል ነው ለማለት ግን አይቻልም ሲሉም አቶ ለማ ተናግረዋል።
በቀጣይም ከነዚህ ችግሮች በመነሳት የተሻሉ ስራዎችን በመስራት ለህብረተሰቡ እርካታ ልንፈጥር ይገባል ሲሉም አዲሱ ርዕሰ መስተዳድር ገልጸዋል።
በመቀጠልም የክልሉን የካቢኔ አባላት እና የተለያዩ የክልሉ መንግስት መስሪያ ቤት ሃላፊዎች ዝርዝርም ለጨፌው በማቅረብ አስፀድቀዋል።
በዚህም መሰረት
1 አቶ ኡመር ሁሴን ፦ የክልሉ ምክትል ርእሰ መስተዳድር
2 አቶ አብይ አህመድ፦ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ልማት እና ቤቶች ቢሮ ሃላፊ
3 አቶ ስለሺ ጌታሁን፦ በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የእርሻ እና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ሃላፊ
4 አቶ ቶሎሳ ገደፋ፦ የክልሉ የገንዘብ እና ኢኮኖሚ ትብብር ቢሮ ሀላፊ
5 አቶ ብርሃኑ ፀጋዬ፦ የክልሉ የፍትህ ቢሮ ሃላፊ
6 ዶክተር ደረጄ ጉደታ፦ የክልሉ የጤና ጥበቃ ቢሮ ሃላፊ
7 ዶክተር ሀሰን የሱፍ፦ የክልሉ የደን እና አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ቢሮ ሃላፊ
8 አቶ ሀብታሙ ሀይለሚካኤል፦ የክልሉ የወጣቶች እና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ
9 አቶ ደመላሽ ገብረሚካኤል፦ የክልሉ የአስተዳደር እና ፀጥታ ቢሮ ሃላፊ
10 ወይዘሮ ሎሚ በዶ፦ የክልሉ የባህልና ቱሪዝም ቢሮ ሃላፊ
11 አቶ አሰፋ ኩምሳ፦ የክልሉ የውሃ፣ ማዕድን እና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊ
12 ወይዘሮ አዚዛ አብዲ፦ የክልሉ የሴቶች እና የህፃናት ቢሮ ሃላፊ
13 አቶ ወንድማገኝ ነገራ፦ የክልሉ ንግድ እና ገበያ ልማት ቢሮ ሃላፊ
14 አቶ ካሳዬ አብዲሳ፦ የክልሉ የቴክኒክና ሙያ ቢሮ ሀላፊ
15 አቶ ብርሃኑ ፈይሳ፦ የርዕሰ መስተዳድሪ ጽህፈት ቤት ቢሮ ሃላፊ
16 አቶ ኤልማ ቃጴ፦ የክልሉ ዋና ኦዲተር
17 ወይዘሮ ሂሩት ቢራሳ፦ የክልሉ የስነ ምግባር እና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር
18 አቶ ጌቱ ወዬሳ፦ የኦሮሚያ ራዲዮ እና ቴሌቭዥን ድርጅት ዋና ዳይሬክተር
ሆነው እንዲሾሙ የቀረቡ ሲሆን፥ ተሿሚዎቹ የዳበረ የሥራ ልምድና የትምህርት ዝግጅት ያላቸው መሆኑን ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ለማ መገርሳ ለጨፌው አቅርበዋል።
የጨፌው አባላት ሹመቱን በሙሉ ድምጽ አጽድቀውታል።
በዛሬው አጨፌ ኦሮሚያ አምስተኛ የሥራ ዘመን ሁለተኛ ዓመት ሁለተኛ አስቸኳይ ስብሰባ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ በመገኘት ሂደቱን ተከታትለዋል።
የጨፌ ኦሮሚያ አምስተኛ የሥራ ዘመን ሁለተኛ ዓመት ሁለተኛ አስቸኳይ ስብሰባ ትናንት የተጀመረ ሲሆን፥ በትናንትና ውሎው በሀገሪቱ የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ ሰፊ ውይይት ማድረጉ ይታወሳል።
በዚሁ ጊዜም የጨፌ ኦሮሚያ ምክትል አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ሮዛ ኡመር ሀገሪቱ ተጋርጦባት በነበረው የሁከት ስጋት ምክንያት የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወደ ቀድሞው ሰላምና መረጋጋት እንድትመለስ እያገዛት ነው ብለዋል።
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤው አቶ አባዱላ ገመዳ ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ለጨፌው ገለፃ ባደረጉበት ወቅት አዋጁ ሰላም ወዳዱን ህብረተሰብ እና ሀገሪቱን ለመጠበቅ ታስቦ የወጣ እንጂ ህዝቡ ላይ ስጋት እንዲፈጠር የወጣ አይደለም ብለዋል።
ይህንንም ጨፌው ተረድቶ ለተወከለበት አካባቢ የማስረዳት እና ለትግበራው የበኩሉን የመወጣት ሀላፊነት አለበት ነው ያሉት።
ከትናንት ጀምሮ ለሁለት ቀናት የተካሄደው የጨፌ ኦሮሚያ አምስተኛ የሥራ ዘመን ሁለተኛ ዓመት ሁለተኛ አስቸኳይ ስብሰባ ዛሬ ተጠናቋል።
በሀይለኢየሱስ ስዩም