Widgetized Section

Go to Admin » Appearance » Widgets » and move Gabfire Widget: Social into that MastheadOverlay zone

በኢትዮጵያ የህዝቡን ጥያቄ ተጠቅመው ሁከት ከሚፈጥሩ ቡድኖች ጀርባ የግብጽ ድጋፍ መኖሩን ምሁራን ተናገሩ

egypt-on-ethiopia
አዲስ አበባ ፣ መስከረም 25 ፣ 2009 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ተጠቅመው ሁከት ከሚፈጥሩ ቡድኖች ጀርባ ሀገሪቱ የተፈጥሮ ሀብቷን እንድትጠቀም የማትፈልገው ግብጽ ድጋፍ አለ ሲሉ ያነጋገርናቸው ምሁራን ተናገሩ።
በኢትዮጵያ መንግስትም ያመነው የሀገሪቱ እድገት የፈጠረውና ለዜጎቿ ያልተሟሉ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች አሉ፤ ሆኖም ይህን የህዝብ ጥያቄ ሌላ አላማ ያላቸው ቡድኖች ለሁከት መፍጠሪያነት እየተጠቀሙበት ስለመሆኑ መንግስት ይገልጻል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝ ከዚህ ጀርባ ሀገሪቱ የተፈጥሮ ሀብቷን እንድትጠቀም የማይፈልጉ አካላት በገንዘብ ጭምር የተሳተፉበት ነው ማለታቸው የሚታወስ ሲሆን፥ የእርሳቸውን ንግግር ያረጋገጠ ጥምረትን የሚያሳይ የተንቀሳቃሽ ምስል በግብጽ መዲና ካይሮ ታይቷል።
በዚች ከተማ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት ከተፈረጀው ኦነግ አባላትና ደጋፊዎች ፊት የተደረገው ንግግር፥ ትግላችሁን እናውቃለን ከሚል መነሻ አሁን ላለው ሁኔታ ግብጽ ድጋፍ እንዳላት ያመለክታል።

ከወራት ወዲህ በሀገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች እየታየ ያለው ሁከት እሁድ እለት በተከበረው የኢሬቻ በዓል ላይ ቀጥሎ አሳዛኝ መጨረሻን አሳይቷል።

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌደራሊዝም መምህርና የሶስተኛ ዲግሪ እጩ ተማሪ የሆኑት አቶ ናሁሰናይ በላይ እንደሚሉት፥ በሀገራት እንዲህ አይነት ጥያቄዎች ሲነሱ ለራሳቸው አላማ ሊጠቀሙበት የሚፈልጉ አካላት መኖራቸው አይደንቅም።

በግብጽ በኩልም የምናየው ነገር የተፈጥሮ ሀብታችን የሆነው የአባይ ወንዝን እንዳናለማ ከመፈለግ የመጣ ነው ይላሉ።

በአባይ ዙሪያ በርካታ ጥናታዊ ጽሁፍ በማቅረብ የሚታወቁት የኮተቤ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የጂኦግራፊ መምህር ረዳት ፕሮፈሰር ብርሀኑ በላቸው ደግሞ፥ ግብጾች በየትኛውም ወቅት ቢሆን አጋጣሚዎችን ከመጠቀም አያልፉም ነው የሚሉት።
አቶ ናሁሰናይ በበኩላቸው፥ በግብጽ መንግስት በተቀየረ ቁጥር የስርዓት ባህሪ በአንድ ጊዜ ይለወጣል የሚል የዋህነት ውስጥ መገባት የለበትም ባይ ናቸው።

ግብጽ በህዳሴው ግድብ ጉዳይ እዚህ ዲፕሎማሲ ላይ የደረሰችውም ኢትዮጵያ በልማት በሰራችው ስራ ያሳደገችውን አለም አቀፍ ተቀባይነት መጋፋት ስለከበዳት መሆኑንም ይናገራሉ።

ከሰሞኑ በግብጽ መገናኛ ብዙሀን የሚሰሙ ነገሮች ኢትዮጵያ ውስጥ ብሄሮችን አማርጦ የመጠቀም አካሄድን ያሳያሉ።
እሁድ እለት አልጋሀድ አል አራቢያ የተሰኘ በግብጽ ያለ የቴሌቪዥን ጣቢያ እንግዳ ጋብዞ ስለ ወቅቱ የኢትዮጵያ ጉዳይ ባወያየበት ወቅት በኢሬቻ በዓል የተከሰተውን ሁከት ደጋግሞ ያሳይ ነበር።
በኢትዮጵያ አማራ እና ኦሮሞ የተሰኙት ብሄሮች በጋራ ስለቆሙ ይህ መንግስት ተጨንቋል፤ ችግሩንም መቋቋም አልቻለም ሲሉም በዜና እወጃ ሰዓቱ እንግዳ ሆነው የቀረቡት ምሁር ያብራራሉ።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህሩ አቶ ናሁሰናይም፥ የቀድሞ መሪዎች የብሄሮች አያያዝ ላይ ያለባቸው ችግር ሊነሳ ይችላል እንጂ የሀገሪቱ ህዝቦች ለሀገራዊ ጉዳይ በአንድ የመቆም ችግር እንደሌለባቸው ያስረዳሉ።

በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ከፍተኛ ተመራማሪ አምባሳደር አብዱልአዚዝ አህመድ፥ በታሪክም ቢሆን ኢትዮጵያ ካጋጠሟት ችግሮች ጀርባ የውሃ ጥያቄ አለን የሚሉት ግብጾች አሉበት ብለውናል።

አሁን ላይ መጨረሻቸው አንድ ፍላጎት ያልሆነ ጥምረት ይታያል፤ በሃገሪቱ ሁከት እንዲፈጠር በሚያደርጉ ሃይሎችና በግብጽ መካከል።

ከተጣማሪዎቹ አንደኛው ኢትዮጵያ ውስጥ መብቴ ስላልተከበረ ነው ያመጽኩት ለመብቴም ነው የምታገለው ይላል፤ በግብጽ በኩል የሚነሳው የሌላኛው ፍላጎት ደግሞ ኢትዮጵያ ተዳክማ ማየት ቢቻልም ስርዓቷ ፈርሶ ማየትን ይመኛል።

እንደ አቶ ናሁሰናይ አባባል ታዲያ ይህ ሊሰምር የማይችል ጥምረት ነው።

የኮተቤ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጁ ረዳት ፕሮፌሰር ብርሀኑም፥ የኢትዮጵያ መንግስትን በሀይል እንጥላለን ካሉ ቡድኖች ጋር የሚፈጥሩት ጥምረትን ጊዜያዊ ብለውታል፤ ህዝቡም ከዚህ ጀርባ ያለውን ጉዳይ ሊረዳ እንደሚገባ በመጥቀስ።

መንግስትም የሀገሪቱን ልማት በማፋጠን በውጭ ጉዳይ ፖሊሲው እንዳለው የውስጥ ተጋላጭነትን በመቀነስ ለውጭዎቹም መድፈን አለበት ብለዋል ምሁራኑ።