Widgetized Section

Go to Admin » Appearance » Widgets » and move Gabfire Widget: Social into that MastheadOverlay zone

ኢትዮጵያ በሱዳን ወደብ ድርሻ ኖሯት በጋራ ለማልማትና ለማስተዳደር ከሀገሪቱ ጋር ተስማማች

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ፣ 25፣ 2010፣ (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያ በሱዳን ወደብ ድርሻን በመያዝ ወደቡን ለማልማት እና በጋራ ለማስተዳደር የሚያስችላትን ስምምነት ከሱዳን ጋር ገባች።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በሱዳን የሁለት ቀናት ጉብኝት በማድረግ ላይ መሆናቸው ይታወቃል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ከሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር ሀሰን አልበሽር ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ በሰጡት መግለጫ፥ የወደብ ልማቱን እና በጋራ የማስተዳደሩ ስራው በፍጥነት ወደ ተግባር እንዲገባ ሀገራቱ መስማማታቸውን ተናግረዋል።

ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ የሱዳን ወደብን ለሰሜን እና ሰሜን ምእራብ አካባቢዎች ስትጠቀም መቆየቷ ይታወቃል።

መሪዎቹ በተጨማሪም ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አንፃር ሱዳን አሁንም ከዚህ ቀደም እንደነበረው ሁሉ ፍትሃዊ ተጠቃሚነትን ያረጋገጠ እና ሁሉም አሸናፊ የሚሆንበት ፖሊሲ እንዲኖር እንደምታምን መግለፃቸውን ነው ያነሱት።

የሀገራቱ የህዝብ ለህዝብ ትስስር እንዲጠናከር በጋራ ድንበር አካባቢ ነፃ የንግድ እንቀስቃሴ እንዲኖር ሁለቱ መሪዎች መስማማታቸውንም ነው ዶክተር ወርቅነህ የተናገሩት።

ዶክተር አብይ በተለያዩ ምክንያቶች በሱዳን እስር ቤቶች የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እንዲፈቱ ያቀረቡትንም ጥያቄ ፕሬዚዳንት አልበሽር የተቀበሉ ሲሆን፥ መፈታታቸው በፍጥነት ተግባራዊ እንዲሆን መሪዎቹ መስማማታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል።

ይህንን ተከትሎም ፕሬዚዳንት ኦማር ሀሰን አልበሽር በሱዳን ማረሚያ ቤቶች የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንን በምህረት ለመፈታት ፕሬዚዳንታዊ አዋጅ አውጥተዋል።

በተለያየ ምክንያት በጥርጣሬ እና በፍርድ ውሳኔ ሱዳን ውስጥ የታሰሩ ሁሉም ኢትዮጵያውያን እንዲለቀቁ ውሳኔ ማሳለፋቸውን ነው ፕሬዝዳንት አልበሽር ተገለፁት።

የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ዜጎቻችን ከእስር እንዲለቀቁ በፕሬዚዳንቱ ለተሰጠው ውሳኔ አመስግነው፤ ለሁለቱ አገሮች ግንኙነት መጠናከር አስፈላጊውን ሁሉ አደርጋለሁ ብለዋል።