Widgetized Section

Go to Admin » Appearance » Widgets » and move Gabfire Widget: Social into that MastheadOverlay zone

የኢህአዴግ ምክር ቤት በቀጣዩ ሳምንት ይሰበሰባል

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 6፣ 2010 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባውን በድርጅቱ አመራር እና በብሄራዊ ድርጅቶቹ መካከል ጠንካራ ትስስር በሚፈጥር መልኩ እየተከናወነ መሆኑን የኢህአዴግ ፅህፈት ቤት ሀላፊ ገለፁ።

ሀላፊው አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደተናገሩት፥ ከእሁድ ጀምሮ የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባውን በማካሄድ ላይ ይግኛል።

ባለፉት አምስት ቀናትም እያንዳንዱ ብሄራዊ ድርጅት በታህሳሱ የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባ ውሳኔዎችን ከየራሱ ተጨባጭ ሁኔታ እንዴት ወስዶ ራሱን እንደተመለከተ የቀረቡትን ሪፖርቶች ሲያይ ቆይቷል።

እስካሁንም የሶስት ብሄራዊ ድርጅቶች ማዕከላዊ ኮሚቴዎች የላኳቸው ሪፖርቶች በዝርዝር መፈተሻቸውን ነው አቶ ሽፈራው ሽጉጤ የገለፁት። ቀሪው የአንድ ድርጅት ሪፖርትም በነገው እለት እንደሚታይ ጠቁመዋል።

ባለፉት ቀናት የተካሄደው የብሄራዊ ድርጅቶች ሪፖርት ግምገማ በጣም ውጤታማ ነበር ያሉት አቶ ሽፈራው፥ ግምገማው የድርጅቱን አንድነት በሚያጠናከር መንገድ ተከናውኗል ብለዋል።

የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በ17 ቀናቱ ግምገማው ያስቀመጣቸው ውሳኔዎች በየብሄራዊ ድርጅቱ የተፈፀሙበትን ጥልቀት እና ይዘት በዝርዝር ፈትሾ እየተቀበለ ሄዷል ነው ያሉት።

በአጠቃላይ ኢህአዴግ ካለበት ሁኔታ ተነስቶ ያስቀመጣቸውን አቅጣጫዎች በየብሄራዊ ድርጅቱ የተተገበረበት፣ አመራሩ የመራበት እና የታዩ ለውጦች ላይ ጠንካራ እና የጠለቀ ውይይት እንደተካሄደ ገልፀዋል።

ስብሰባው በድርጅቱ አመራር እና በድርጅቶቹ መካከል ጠንካራ ትስስር በሚፈጥር መልኩ እየተከናወነ መሆኑን በማንሳትም እስካሁን የዓላማ አንድነት መፍጠር የቻለም ነው ብለዋል።

ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው አሁን እያካሄደ ያለውን ስብሰባ እንደጨረሰም፥ በታህሳሱ ስብሰባ ማግስት የተቋቋሙ ግብረ ሀይሎች የደረሱበት የለውጥ ስራ ያለበትን ሁኔታ እንደሚገመግም አቶ ሽፈራው አስታውቀዋል።

በመቀጠልም የኢህአዴግ ምክር ቤት የሚነጋገርበት ሪፖርት ላይ ስራ አስፈፃሚው ተወያይቶ ለምክር ቤቱ ያደራጃል ብለዋል።

በሚቀጥለው ሳምንት መጀመሪያ ምናልባትም ከማክሰኞ ወይም ረቡዕ ጀምሮ የኢህአዴግ ምክር ቤት ተሰብስቦ የእስካሁኑን ግምገማ ሪፖርቶች ከተመለከተ በኋላ የተፈጠረውን የአመራር ክፍተት እንደሚያሟላም አስታውቀዋል።