Widgetized Section

Go to Admin » Appearance » Widgets » and move Gabfire Widget: Social into that MastheadOverlay zone

ብሄራዊ የደህንነት ምክር ቤት የሚከሰቱ ግጭቶችን ለመፍታት እቅድ አውጥቶ እንቅስቃሴ ጀምሯል-ጠ/ሚ ኃይለማርያም


አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 30፣ 2010 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ብሄራዊ የደህንነት ምክር ቤት በአገሪቱ የሚከሰቱ የሰላምና ፀጥታ መደፍረስ እንዲሁም ግጭቶችን ለመፍታት እቅድ አውጥቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ገለፁ።

ምክር ቤቱ እነዚህን ችግሮች ለመፍታት ህዝቡን በዋናነት በማሳተፍ ላይ አተኩሮ እንደሚሰራ እና ይህም ተከታታይ የህዝብ ውይይቶችን እንደሚያጠቃልል ነው ያነሱት።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ዛሬ ለጋዜጠኞች ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫው ላይ የፌደራል እና የክልል የፀጥታ አካላት በተቀናጀ ሁኔታ ያለአግባብ መጠቀም የሚፈልፈጉ አካላትን ከዚህ ድርጊታቸው ለማስቆም እና በዘላቂነት ይህን ድርጊት ለማጥፋት እንዲሁም ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ከዚህ ሳምንት ጀምሮ ስራ መጀመሩን አንስተዋል።

በኦሮሚያ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች አንዳንድ አዋሳኝ አከባቢዎች ላይ የተከሰተውን ግጭት ተከትሎ የተፈናቀሉ፥ በ100 ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎችን በዘላቂነት ለማቋቋም ግብረሃይል ተቋቁሞ በቀናት ውስጥ ስራውን ይጀምራል ብለዋል።

አገሪቱ በአሁኑ ወቅት በሰላማዊ ሁኔታ ውስጥ እንደምትገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም አረጋግጠዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኦሮሚያ እና ኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ግጭት ከተፈጠረ በኋላ በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች እና አጋር ድርጅቶች መካከል መስማማቶች የሉም ልዩነቶች ይሰታዋላሉ የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምላሻቸው እየታየ ያለው ችግር በፓርቲዎች መካከል ሳይሆን አመራሩ ላይ ነው የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

የትኛውም አካባቢ ያለ ህዝብ የእኔ ህዝብ ነው ብሎ ያለማሰብ የአቋም ችግር አለ ብለዋል።

ይህም ችግር የሁሉም የኢህአዴግ አባል እና አጋር ድርጅቶች ችግር መሆኑን ነው የጠቆሙት።

በሌላ በኩል የፀጥታ አካላት ማስከበር ያለባቸውን ህገመንግስቱን እና ህገመንግስታዊ ስርዓቱን ሆኖ ሳለ ጥቂት የፀጥታ አካላት በደም እና በጎሳ ለይቶ ህዝብን የማየት አዝማሚያ እንደተስተዋለባቸው ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ አንዳንድ የፀጥታ አካላት በግጭት ውስጥ ተሳትፈው በመገኘታቸው እርምጃ ተወስዶባቸዋል ብለዋል።

በዚህ ድርጊት ውስጥ የተገኙትን አካላት ተጠያቂ ማድረጉ ተከታታይ ስራን እንደሚጠይቅም ነው የገለፁት።

በኢህአዴግ ውስጥ ይፋ ስለማይደረግ እንጂ ቀድሞም የሀሳብ ትግል መኖሩን በመናገር፥ ሁሌም ግን ያሸነፈው ሀሳብ ተግባራዊ እንደሚሆን ተናግረዋል።

ሆኖም መረጃን ከመስጠት አንፃር በመንግስት በኩል ያለው ችግር ህዝቡን በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ለሚናፈስ አሉባልታና የሀሰት ፕሮፖጋንዳ እንዳጋለጠው አምነዋል።

“የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በመካከላቸው ልዩነት ይታያል” ለሚለው ጥያቄም፥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሰሞኑ አባል ድርጅቶቹ ያደረጉት ኮንፍረንስን በማሳያነት በማቅረብ “የተለያየ ፓርቲ እንዴት በተለያየ ኮንፍረንስ ላይ ተመሳሳይ ሀሳብ ያንፀባርቃል?” በሚለው ጥያቄያቸው መልስ ሰጥተዋል።

“ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ክልሎች ከፌደራል መንግስቱ ይልቅ ጠንክረው እየወጡ ነው፤ ይህ እንዴት ይታያል?” በሚል ለቀረበው ጥያቄ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ ይህ ደስታችን ነው የሚል ሆኗል። ህገ መንግስቱ ይክልሎችን እና የፌደራል መንግስትን ስልጣንን ለይቶ ያስቀመጠ መሆኑን ገልፀዋል።

በፌደራል መንግስቱ ድጎማ የሚንቀሳቀሱት ክልሎች በሚፈለገው ደረጃ ጠንክረው አልወጡም ባይ ናቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

በአጎራባች ክልሎች መካከል እየተካሄደ ያለው የህዝብ ለህዝብ ኮንፍረንስም በክልሎች ብቻ ሳይሆን በፌደራል መንግስት እቅድ ውስጥም ነበረ ብለዋል።

በኦሮሞ እና አማራ ህዝቦች መካከል የተጀመረው ለዚህ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፥ ይህ በቀጣይ በሁሉም ተጎራባች ክልሎች መካከል እንደሚቀጥል እና ይህም በመጨረሻ ወደ ሀገር አቀፍ ኮንፍረንስነት እንደሚመጣ ጠቁመዋል።

ኢህአዴግ በእርግጥ በጥልቀት መታደሱን ጨርሷል ወይ?

ከዚህ ቀደም ኢህአዴግ በነበሩትን የተሃድሶ ሂደቶች ሲያስታውሱ፥ ጥገኛው ባለሃብት በመንግስት ባለስልጣናት ላይ ተጣብቆ የመበልፀግ ፍላጎት የታየበትን አካሄድ ለማረም የታለፈባቸው መሆኑን አንስተዋል።

አሁን ላይ ግን የኪራይ ሰብሳቢነት የፖለቲካ ኢኮኖሚ ጥቅሙን ለማስከበር ህዝብን ከህዝብ እስከማጋጨት ደርሷል ነው ያሉት። ለዚህም በቅርቡ አወዳይ ላይ የነበረውን ሁኔታ በምሳሌነት አንስተዋል።

በዚህ አካባቢ ላይ የነበረው ግጭት መነሻ ቦታው ጫት በዋነኝነት የሚመረትበት እንደመሆኑ መጠን፥ ከዚህ ምርት አምራቹ እንዳይጠቀም መፈለጋቸው ነው ብለዋል።

በአጠቃላይ ምንም እንኳ ኢኮኖሚው ቢያድግም አብሮት ያረገዘው ችግር አለ በማለት ይህም ችግር ኪራይ ሰብሳቢነት መሆኑን አመልክተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የልማታዊ ፖለቲካ ኢኮኖሚ በኪራይ ሰብሳቢነት ላይ የበላይነቱን እስከሚያረጋግጥ ድረስ ኢህአዴግ የጀመረውን በጥልቀት የመታደስ ሂደት እንደሚቀጥል ነው የተናገሩት።

የሼክ መሀመድ ሁሴን አሊ አል አሙዲ ጉዳይ

ሳዑዲ አረቢያ ከሙስና ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ስር ካዋለቻቸው ግለሰቦች መካከል አንዱ የሆኑት ትውልደ ኢትዮጵያዊው ቢሊየነር የሼክ መሀመድ ሁሴን አሊ አል አሙዲንን በተመለከተ መንግስት በዲፕሎማሲያዊ መልኩ ጉዳዩን አስመልክቶ መረጃን እየተከታተለ መሆኑን ጠቁመዋል።

ይህን ተከትሎ በኢትዮጵያ ባለው የእሳቸው ኢንቨስትመንት ላይ እክል ይፈጠራል ብሎ መንግስት እንደማያምንም ነው የገለፁት።

ከዚህ ውጭ ግን ሳዑዲ አረቢያ ሉዓላዊ ሀገር እንደመሆኗ ከኢትዮጵያ መንግስት በኩል ሌላ ሊሰራ የሚችል ነገር እንደሌለ አስታውቀዋል።